የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት አያያዝ እንዲስተካከል እንግሊዝ ጥያቄ አቀረበች
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢትዮጵያ እየተከሰተ ካለው ቀውስ ጋር ተያይዞ እየተፈጠሩ ያሉ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ችግሮች እንዲስተካከሉ እንግሊዝ ጠየቀች፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ሒሩት ዘመነ ከእንግሊዝ አምባሳደር ሱዛና ሞርሄድና ከኤምባሲው የሥራ ኃላፊዎች ጋር ውይይት ባደረጉበት ወቅት ባለፉት ሁለት ዓመታት በአገሪቱ እየተከሰተ ካለው ቀውስ ጋር ተያይዞ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ችግር እንዳለ፣ ኢትዮጵያም ይህን ችግር እንድታስተካክል እንግሊዝ ምክረ ሐሳብ ማቅረቧ ታውቋል፡፡ ይህ ምክረ ሐሳብ የቀረበው ኢትዮጵያና እንግሊዝ ለአራተኛ ጊዜ በሰብዓዊ መብቶች ላይ ያተኮረ የጋራ ውይይት፣ ሰኞ ኅዳር 4 ቀን 2010 ዓ.ም. በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በተካሄደበት ወቅት ነው፡፡ በውይይቱ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ሒሩት ዘመነ፣ በኢትዮጵያ የስደተኛና ከስደት ተመላሽ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ተወካዮች፣ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ተወካዮች፣ በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ሱዛና ሞርሄድና የኤምባሲው የሥራ ኃላፊዎች፣ የብሪታኒያ ዓለም አቀፍ የልማት ድርጅት (ዲኤፍአይዲ) ዳይሬክተሮችና ሌሎች የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ተገኝተው ነበር፡፡ የውይይቱ አጀንዳዎችም የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት አያያዝ፣ ስደት፣ የመንግሥት ተጠያቂነትና ግልጽነት ነበሩ፡፡ የሁለቱ አገሮች የጋራ ውይይት የተካሄደው በዝግ ቢሆንም፣ የሪፖርተር ምንጮች እንደጠቆሙት በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት አያያዝ ላይ ያሉ ችግሮችን የእንግሊዝ መንግሥት ተወካዮች በዝርዝር አውስተዋል፡፡ አንድ የእንግሊዝ ዲፕሎማት ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያ በምሥራቅ አፍሪካ ስደተኞችን በማስተናገድ ግንባር ቀደም አገር ብትሆንም በሰብዓዊ መብት አያያዝ ላይ ችግሮች አሉባት፡፡ ‹‹ይህንን ያህል የስደተኛ